የርገን ክሎፕ እግር ኳስ ናፍቆኛል ብለዋል የሊቨርፑሉ አሰልጣኝ የርገን ክሎፕ “ወደ ልምምድ ሜዳ በመመለሳቸው ” ደስተኛ መሆናቸውን ተናግረዋል። በመጪው ሰኔ 17 ከቆመበት ለሚቀጥለው የፕሪምየር ሊግ ውድድር ለመዘጋጀት “ከድንቁ የእግር ኳስ ቡድን ” ጋር በመገናኘቴ ደስተኛ ነኝ ብለዋል።
የክሎፕ ቡድን በ25 ነጥብ ልዩነት የደረጃ ሰንጠረዡን እየመራ ይገኛል። ከ30 ዓመት በኋላ የክለቡን የመጀመሪያ የፕሪምየር ሊግ ዋንጫ ለማንሳት ከጫፍ ደርሷል። ፕሪምየር ሊጉ በኮሮና ቫይረስ ስርጭት ምክንያት የተቋረጠው ባለፈው መጋቢት 13 መሆኑ ይታወቃል። “ለማመን ያስቸግራል። እግር ኳስ በጣም ናፍቆኝ ነበር” ብለዋል ክሎፕ ከቢቢሲ ጋር ባደረጉት ቆይታ። “በህይወት እጅግ አስፈላጊው ነገር እንዳልሆነ አውቃለሁ። ነገር ግ በጥልቅ ፍቅር የምወድደው ነገር ነው። ሰዎችም በናፍቆት ይጠብቁታል ብዬ አስባለሁ። ” ብለዋል።
በሰኔ 17 ከሚደረጉት ሁለት ጨዋታዎች አንዱ ማንቸስተር ሲቲን ከአርሰናል የሚያገናኘው ነው። አርሰናል ይሄንን ጨዋታ ካሸነፈ ሊቨርፑል በመጀመሪያ ጨዋታው አሸናፊ ከሆነ ዋንጫውን ያነሳዋል። አለበለዚያ እስከሚቀጥለው ሳምንት ጨዋታ መጠበቅ ይኖርበታል። ክሎፕ ግን ” ገና ብዙ ሊሰሯቸው የሚገቧቸው ነገሮች መኖራቸውን ይናገራሉ። “ሊቨርፑል የቻለውን ያህል ብዙ ጨዋታዎችን ማሸነፍ ይፈልጋል ” ብለዋል። “ስለ ዋንጫው ማሰብ አንዳች አስደሳች ስሜት ይፈጥራል። ነገር ግን ገና ሻምፒየን አልሆንም” ሲሉ ያክላሉ ። “በጣም መቃረባችንን እናውቃለን። መቅረብ ግን ማሸነፍ አይደለም። ልናሳካቸው የምንችላቸው 27 ነጥቦች ይቀራሉ ።
በቻልነው አቅም ሁሉንም ነጥብ ለመውሰድ እንሞክራለን። ቀጣዮቹ ጨዋታዎች በሙሉ በዝግ ስታዲየም የሚከናወኑ ናቸው። የሊቨርፑሉ አምበል ጆርዳን ሄንደርሰን ባለፈው ሳምንት ከቢቢሲ ራዲዮ 5 ጋር ባደረገው ቆይታ የፕሪምየር ሊጉን ዋንጫ ያለ ደጋፊዎች ማንሳት አንዳች እንግዳ ስሜት እንደሚፈጥር ተናግሮ ነበር። ክሎፕም የአምበሉን አስተያየት የሚጋሩ ይመስላል። “ደጋፊዎች መሰብሰብ የሚችሉበት ጊዜ ሲመጣ አጋጣሚውን በጋራ እናከብረዋለን ” ብለዋል።
ውድ አድማጮቻችን እና ተከታዮቻችን የኢትዮ ኤፍ ኤም ስርጭቶችን፣ዜናዎችን እና ሌሎች ዝግጅቶችን ለመከታተል የቴሌግራም ቻናላችንን ይቀላቀሉ።
በአቤል ጀቤሳ
ግንቦት 25 ቀን 2012 ዓ.ም











