የሚድሮክ ኢትዮጵያ ባለቤትና ሊቀመንበር ሼክ መሐመድ ሁሴን አሊ አል-አሙዲ ዘሬ በአዲስ አበባ ድርጅታቸውን እንደገና በማደራጀት ሥራ አስፈፃሚዎችን ሾመዋል።
የኩባንያው ባለቤት ሼክ መሐመድ ላለፉት በርካታ ሳምንታት አዲስ መዋቅር ሲያስቡና ሲያስጠኑ ከቆዩ በኋላ አዲሱን መዋቅር ይፋ አድርገዋል፡፡
በዚሁ መሠረት ሚድሮክን በኢትዮጵያ ወክለው በዋና ስራ አስፈፃሚነት እንዲያገለግሉ አቶ አብነት ገብረመስቀልን ሾመዋል፡፡
አቶ አብነት በተጨማሪም ከባለሀብቱ ኩባንያዎች በኮንስክትራክሽን፣ በሆቴሎች እና በሪል ስቴት ዘርፍ ያሉትን ኩባንያዎች በሙሉ እንዲመሩ መድበዋቸዋል፡፡
በተጨማሪም የመድሀኒት ፋብሪካቸውን ፋርማኪዩርን እየመሩ እንዲቀጥሉም ወስነዋል፡፡
ከዚህ በተጫማሪ አቶ ጀማል አህመድን በዋና ሥራ አስፈፃሚነት ደረጃ በማንፋክቸርንግ፣ በማዕድን፣ በንግድ፣ በግብርና እና በአግሮ ፕሮሰሲንግ ዘርፍ ያሉትን ኩባንያዎች እንዲመሩ መሾማቸውን ካፒታል ዘግቧል፡፡
ደርባ ሲሚኒንቶ ፋብሪካን ደግሞ አቶ ሀይሌ አሰግዴ እየመሩ እንዲቀጥሉና ሌሎች ኩባንያዎችም በነበሩበት ተጠናክረው እንዲቀጥሉ የሚያስችል አዲስ መዋቅር ይፋ ያደረጉት ባለሀብቱ ኩባንያዎቻቸው ለኢትዮጵያ እድገት እንደወትሮው
ሁሉ መስራታቸውን እንዲቀጥሉ መመሪያ መስጠታቸው ተገልጿል።
ሚድርክ ኢትዮጵያን ከ20 ዓመት በላይ የኩባንያዎቹ ዋና ስራ አስፈፃሚ ሆነው ያገለገሉት ዶክተር አረጋ ይርዳው ከሁለት ወር በፊት ከሃላፊነት መነሳታቸው ይታወሳል።
አቶ ጌታቸው ሀጎስ ዶክተር አረጋን ተክተው የሚድሮክ ቴክኖሎጂ ግሩፕ ኩባንያዎች ጊዜያዊ ዋና ስራ አስፈፃሚ ሆነው ሲሰሩ ቆይተው ነበር።
ሚድሮክ ቴክኖሎጂ ግሩፕ 80 የሚድሮክ ኢትዮጵያ እህትና ተባባሪ ኩባንያዎች ያሉት ሲሆን፥ እነዚህም ኩባንያዎች በግብርና፣ በአግሮ ኢንዱስትሪ፣ በግንባታ፣ በሆቴልና ቱሪዝም፣ በማምረቻ ኢንዱስትሪ፣ በማእድን ልማት፣ በነዳጅና ጋዝ፣ በሪል ስቴት፣ በንግድ፣ በጤና፣ በትምህርትና ስልጠና ዘርፎች ላይ ተሰማርተው ይገኛሉ።
ውድ አድማጮቻችን እና ተከታዮቻችን የኢትዮ ኤፍ ኤም ስርጭቶችን፣ዜናዎችን እና ሌሎች ዝግጅቶችን ለመከታተል የቴሌግራም ቻናላችንን ይቀላቀሉ። https://t.me/ethiofm107dot8
ኢትዮ ኤፍ ኤም የኢትዮጵያዊያን
ሰኔ 10 ቀን 2012 ዓ.ም











