የክልል ታርጋ ያላቸው ባለ ሁለት እግር ተሽከርካሪዎች በአዲስ አበባ ሲንቀሳቀሱ ካገኘ እንደሚወርስ የከተማዋ ትራንስፖርት ቢሮ አስታወቀ።

በቢሮው ፍቃድ ከተሰጣቸው ሞተረኞች ውጪ የክልል ታርጋ ቢኖራቸው እንኳን ማንኛውም ሞተረኞች በመዲናዋ መንቀሳቀስ እንደማይችሉ ነው ቢሮው ያስታወቀው።

በተጨማሪም በቢሮው ተደራጀተው አሁን ላይ እየሰሩ ከሚገኙት ሞተረኞች ውጪ የኮድ 2 ም ሆነ የኮድ 3 ሞተር ሳይክሎች ፍቃድ መስጠት መቆሙን ቢሮ አሳውቋል።

የቢሮ ሀላፊው አቶ ስጦታ ጣሰው በ2011 የወጣውን የባለ ሁለት ተሽከርካሪዎች ላይ የወጡ መመሪያ ቁጥር 2 እና ቀጥር 3 ላይ የተደረጉ ማሻሻያዎች ላይ መግለጫ ሰጥተዋል።

መመሪያው በቢሮው ፍቃድ ከተሰጣቸው ውጪ በከተማዋ የክልል ታርጋ ለጥፈው የሚንቀሳቀሱ ሞተረኞች ላይ ስለሚወሰደው እርምጃ ግልፅ ነገር እንዳልነበረው በዚህም የተነሳ ሞተረኞች የክልል ታርጋን አስመስለው በመስራት እንደ ባንክ ያሉ እና የተለያዩ የንግድ ተቋማት ላይ ትኩረት አድርገው ዝርፊያ ይፈፅሙ እንደነበር ተናግረዋል።

ይህንን ክፍተት በመገምገምም የክልል ታርጋ ያላቸው ሞተረኞች በመዲናዋ ሲንቀሳቀሱ ከተገኙ ንብረታቸው እንዲወረስ እና ለፍርድ እንዲቀርቡ በመመሪያው በግልፅ መቀመጡን ቢሮ ሀላፊው ተናግረዋል።

ከዚህ ቀደም በመዲናዋ የባለ ሁለት እግር ተሽከርካሪዎች በከተማዋ ለደረሱ የትራፊክ አደጋዎች ከፍተኛ አስተዋፆ ኖሮአቸው በመገኘቱ፣ የከተማዋን የትራፊክ እንስቃሴ በማወካቸው እንዲሁም ባለፊት 2 ዓመታት በሞትር ሳይክል ከቀላል ንጥቂያ እስከ ከባድ ወንጅል በመፈፀሙ መመሪያው 2011 ዓ.ም ላይ መውጣቱን አስታውሰዋል።

በመመሪያው መሰረት በከተማዋ የሚንቀሳቀሱ ሞተረኞች በማህበር እንዲደራጁ እና በግልፅ የሚታይ ታርጋ እንዲለጥፉ፣ ዩኒፎርም እንዲኖራቸው እና ለቁጥጥር ያመች ዘንድ ጂፒኤስ እንዲገጠምላቸው በማድረግ ከ3ሺ 600 በላይ አባላት ያሉት 56 የሞተረኞች ማህበራት ተደራጅተው በከተማዋ እንዲንቀሳቀሱ ፍቃድ ተሰጥቷቸዋል።

ውድ አድማጮቻችን እና ተከታዮቻችን የኢትዮ ኤፍ ኤም ስርጭቶችን፣ዜናዎችን እና ሌሎች ዝግጅቶችን ለመከታተል የቴሌግራም ቻናላችንን ይቀላቀሉ። https://t.me/ethiofm107dot8

በትግስት ዘላለም
ሐምሌ 15 ቀን 2012 ዓ.ም

FacebooktwitterredditpinterestlinkedinmailFacebooktwitterredditpinterestlinkedinmail

Leave a Reply

Your email address will not be published.