በተመጣጠነ ዋጋ ዳቦ ለኅብረተሰቡ ለማቅረብ እንዲችል ታስቦበት ሥራ የጀመረው ይህ ፋብሪካ በሰዓት 80 ሺህ ዳቦ ያመርታል በሚል ነበር፡፡
ባለፈው ሰኔ ወር ተመርቆ አገልግሎቱን በመስጠት ላይ የሚገኘው ፋብሪካው በአሁኑ ሰዓት የታሰበውን ያክል እያመረተ ይሆን? ስንል ጠይቀናል።
የፋብሪካው ስራ አስኪያጅ አቶ ሃይሉ ቡልቡላ እንደነገሩን ፋብሪካው በሰዓት 80 ሺህ የማምረት አቅም ቢኖርም በአሁኑ ሰዓት እያመረተ ያለው ግን በሰዓት ከ30-35 ሺህ ነው ብለዋል፡፡
ፋብሪካው አሁን ላይ በቀን 700 ሺህ ገደማ ዳቦ በማምረት ላይ መሆኑንም ነግረውናል።
የምርት ሂደቱ የታሰበውን ያክል በፍጥነት ያልሄደበት ምክንያት ምድን ነው? ብለን ላነሳንላቸው ጥያቄ የኮሚሽን ስራዎች ባለመጠናቀቃቸው መሆኑን ተናግረዋል።
በቅርቡም ከውጪ በሚገቡ ባለሙያዎች አማካኝነት ይህንን ሂደት ለማጠናቀቅ ስራዎች እየተሰሩ መሆናቸውና ይህ ሲጠናቀቅ ፋብሪካውም ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ ወደ ስራ እንደሚገባ ነግረውናል፡፡
ይህ እንዳለ ሆኖ ግን የሸገር ዳቦ በሚሰራጭባቸው የመሸጫ ሱቆች ከነዋሪዎች ውጪ ዳቦ ቸርቻሪዎች በዝቅተኛ ዋጋ ገዝተው ዋጋ ጨምረው የሚሸጡ ነጋዴዎች እንዳሉ አስተያየታቸውን ለኢትዮ ኤፍ ኤም የሰጡ ሸማቾች ተናግረዋል።
በየዉልሰዉ ገዝሙ
ሐምሌ 22 ቀን 2012 ዓ.ም











