በዎላይታ ዞን ወቅታዊ የፀጥታና የፖለቲካ ሁኔታ የተሰጠ መግለጫ!
የዎላይታ ህዝብ እንደ ሁሉም ኢትዮጵያዊ በሃገራችን በዘመናዊ አገረ ግንባታ ታሪክ ከፍተኛ አስተዋፅኦ ያበረከተ፥ ለአገር ሉዓላዊነት መስዋዕትነት የከፈለ፥ ማንነቱን ያስጠበቀና አኩሪ ታሪክ ያለዉና አሁንም ጠላቴ ድህነትና ኃላቀርነት ብሎ የሚጋፈጥ ከእህት እና ወንድም ኢትዮጵያዊን ህዝቦች ጋር በሠላምና በፍቅር የሚኖር ህዝብ ነዉ።እንደሌሎች ህዝቦች በባለፉት ሥርዓታት ብዙ መሠረታዊ ጥያቄዎች ያልተመለሱለት እንዲሁም የሠላም፥ የልማት እና የዴሞክራሲ ጥያቄዎች እንዲመለሱለት በህጋዊ መንገድ እየታገለ ያለና በአሁኑ ወቅት በአገራችን የተጀመረዉን የለዉጥና የብልፅግና ጉዞ ሻማ በመለኮስና በማቀጣጠል የለዉጥ ሐዋርያና ባለቤት የሆነ ህዝብ ነዉ።
በክልላችን ከተነሱ የመብት ጥያቄዎች ዉስጥ አንዱ በክልል የመደራጀት ጥያቄ ለረጅም ጊዜያት ሲነሳ የቆየ እና ተገቢዉ ምላሽ ሣያገኝ የሰነበተ እንደሆነ ይታወቃል። ነገር ግን ይህንን ጥያቄ በአዲስ አስተሳሰብ አገሪቱን እየመራ ያለዉ ብልፅግና ፓርቲ፥ የህዝቡ ጥያቄ በዴሞክራሲያዊ መንገድ መመለስ አለበት ብሎ ወስኖ፥ በራሱ በህዝቡ ፍላጎት ምላሽ እንዲያገኝ በተደራጀ መንገድ እየሰራ እንደሚገኝ እሙን ነዉ።በክልል የመደራጀት ጥያቄ ምላሽ እንዲያገኝ በብልፅግና ፓርቲ እና በመንግስት ከፍተኛ ርብርብ በሚደረግበት በአሁኑ ወቅት ዎላይታ ዞንን እንዲመሩ ኃላፊነት የወሰዱ አመራሮች ከፓርቲዉ ዲስፒሊንና ከተሰጣቸዉ ህዝባዊና መንግስታዊ ኃላፊነት በተቃራኒ በመቆም የህዝቡን ጥያቄ ሽፋን በማድረግ ለዉጡን ለማደናቀፍ በግልፅና በህቡዕ ተደራጅቶ ከሚንቀሳቀሱ የዉስጥ እና የዉጪ ኃይሎች ጋር እየሰሩ እንዳሉ ተረጋግጧል።
በዚህም ለዉጡን በጉልበት ለመቀልበስ የተለያዩ ታክቲኮችን በመንደፍ፥ በክልል የመደራጀት ጥያቄ አመላለስ ለማወሳሰብ አቅደዉ በመፈፀም በዞኑ ያለመረጋጋትና የንጹሃን ዜጎች ህይወት እንዲቀጠፍ ምክንያት ሆነዋል። በመሆኑ በዎላይታ ዞን የዞኑ ብልፅግና ፓርቲ አስተባባሪ ኮሚቴ አባላት ከፓርቲዉና ከመንግስት ሥራ ኃላፊነት ከነሃሴ 14 ቀን 2012 ዓ/ም ጀምሮ ከኃላፊነታቸዉ እንዲነሱ የክልሉ የብልጽግና ፓርቲ አስተባባሪ ኮሚቴ ወስኗል።ከዞን ጀምሮ በየደረጃዉ የምትገኙ ጠቅላላ አመራሮች፥ ወቅታዊዉን የህዝብ ጥያቄ መሪዉ ብልጽግና ፓርቲ እና መንግስት ባጠረና ጊዜና በህጋዊ መንገድ እንዲመለስ በተስማማነዉ መሠረት፥ መላዉን ህዝብ ባሳተፈና ባለቤት ባደረገ መንገድ ለመፍታትና ከዳር እንዲደርስ ለማድረግ ከክልሉ መንግስትና ከፓርቲዉ ጋር በመቀናጀት መስራት ለምርጫ የሚቀርብ ጉዳይ አይደለም።ስለዚህ ይህንን በመገንዘብ በዞኑ የፓርቲዉን የለዉጥ እንቅስቃሴ የሚያደናቅፍና የሁከትና የብጥብጥ ኃይሎች ሴራ በማክሸፍ የተጀመረዉ የብልፅግና ጉዞ ለአፍታም እንዳይደናቀፍ ኃላፊነታችሁን እንድትወጡ ፓርቲዉ ጥሪ ያቀርብላችሗል። አመራራችን ከመንግስትና ከፓርቲዉ የተጣለበትን ኃላፊነት ወደ ጎን በመተዉ በህገ ወጥ መንገድ የሚደረጉ ማናቸዉም እንቅስቃሴዎች የማይታገስ መሆን ታዉቆ በፓርቲው በዲስፒሊን እንዲፈፅም እናሳስባለን።
መላዉ የዎላይታ ዞን ህዝቦች፥ ወጣቶች፥ የብልፅግና ፓርቲ አባላትና ደጋፊዎች እንዲሁም ከሃገር ዉጪ የምትገኙ የዞኑ ተወላጆች፤ በሃገራችን የተጀመረዉን ለዉጥ እዉን እንዲሆንና ለአፍታም ቢሆን እንዳይደናቀፍ ከፍተኛ ርብርብ ስታደርጉ ቆይታችሃል። ነገር ግን ይህንን ለዉጥ ለማደናቀፍ ከምን ጊዜም በላይ የለዉጥ አደናቃፊ ኃይሎች እየተረባረቡ ይገኛሉ። ስለሆነም ይህንን በህዝቡ ብርቱ ጥረት እየተመዘገበ ያለዉ የለዉጥ ትሩፋት ለማደናቀፍ ያለሙና የሚያሴሩ ኃይሎች በማጋለጥና በመታገል የህዝባችን ጥያቄ ባጠረ ጊዜ በሠላማዊ መንገድ እንዲመለስ በሚደረገዉ ርብርብ ከፓርቲያችንና ከመንግስት ጎን እንድትሰለፉ በአክብሮት ጥሪ ያስተላልፋል።የብልጽግና ጉዟችን በሴረኞች አይደናቀፍም!!!!
የደ/ብ/ብ/ህ ክልል ብልፅግና ፓርቲ ፅ/ቤት











