በመተከል ዞን ማንዱራ ወረዳ ዛሬ ረፋድ ታጣቂዎች በህዝብ ማመላለሻ ተሽከርካሪ ላይ ባደረሱት ጥቃት ሰባት ሰዎች ላይ ቆሰሉ።

በቤኒሻንጉል ጉምዝ ክልል መተከል ዞን ማንዱራ ወረዳ ኤዲዳ በተባለ ቀበሌ በአካባቢው የሚንቀሳቀሱ ታጣቂዎች በህዝብ ማመላለሻ ተሸከርካሪ ላይ በከፈቱት ተኩስ በ7 ሰዎች ላይ ከባድ እና ቀላል ጉዳት መድረሱ ተገለፀ፡፡

የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ኢንስፔክተር ምስጋና ኢንጂፈታ ለኢትዮ ኤፍ ኤም እንደገለፁት ዛሬ ጠዋት ከቻግኒ ወደ ግልገል በለስ ከተማ በመጓዝ ላይ የነበረ የህዝብ ማመላለሻ ተሸከርካሪ ማንዱራ ወረዳ ኤዲዳ የተባለ ቀበሌ እእንደደረሰ በሽፍቶች ተኩስ ተከፍቶበታል፡፡
በጥቃቱም 1 ከባድ ጉዳት እና 6 ቀላል ጉዳት የደረሰ ሲሆን ዜናውን እስካጠናቀርንበት ጊዜ ድረስ የሞተ ሰው አለመኖሩን ገልፀዋል፡፡

በጥይት ተመተው ጉዳት የደረሰባቸው ዜጎች በፓዊ ሆስፒታል ህክምና እየተደረገላቸው እንደሚገኝ ኢንስፔክተር ምስጋና ነግረውናል፡፡

ጥቃት አድራሾችን በቁጥጥር ስር ለማዋል መከላከያ ሰራዊት ፤ ፖሊስ እና የፀረ-ሽምቅ ሀይል በአካባቢው ደርሶ አሰሳ እያደረገ መሆኑን ነግረውናል፡፡

ምክትል ፖሊስ ኮሚሽነሩ ምስጋና እንደገለፁት ከትናንት በስቲያም በተመሳሳይ ቦታ ላይ በህዝብ ማመላለሻ ተሸከርካሪ ላይ ተኩስ ተከፍቶ እንደነበር ገልፀው በሰዎች ላይ ምንም ጉዳት እንዳልደረሰ ለጣቢያችን አረጋግጠዋል፡፡

በክልሉ መተከል ዞን ላይ እየተንቀሳቀሱ የሚገኙ ፀረ-ሰላም ሀይሎች አሁን ላይ በተበታተነ ሁኔታ የሚገኙ ሲሆን አልፎ አልፎ በተሽከርካሪ መኪኖች ላይ ጥቃት የመሰንዘር ሁኔታዎች እየተስተዋሉ ነው ብለዋል፡፡

እነዚህ ሀይሎች ይህንን እንቅስቃሴያቸውን ከማቆምም ባለፈ የክልሉ መንግስት ባስቀመጠው ጊዜ ገደብ ውስጥ እጅቸውን እንዲሰጡ አስጠንቅቀዋል፡፡

ውድ አድማጮቻችን እና ተከታዮቻችን የኢትዮ ኤፍ ኤም ስርጭቶችን፣ዜናዎችን እና ሌሎች ዝግጅቶችን ለመከታተል የቴሌግራም ቻናላችንን ይቀላቀሉ። https://t.me/ethiofm107dot8

በደረሰ አማረ
ሕዳር 23 ቀን 2013 ዓ.ም

FacebooktwitterredditpinterestlinkedinmailFacebooktwitterredditpinterestlinkedinmail

Leave a Reply

Your email address will not be published.