አብዛኛው የሎሊፖፕ እና የከረሜላ አምራቾች ከአመራረት ሂደቱ ጀምሮ እስከ አስተሻሸግ ድረስ የጥራት ችግር ያለባቸው መሆኑ ተገልጿል።
በኢትዮጲያ ምግብ እና መድሃኒት ቁጥጥር ባለስልጣን ባለሙያ የሆኑት ወ/ሪት ህሊና ተስፋዬ እንዳሉት በፋብሪካዎቹ በተደረገ ድንገተኛ ፍተሻ የጥራት ችግር መኖሩን አረጋግጠናል ብለዋል።
በአጠቃላይ በኢትዮጵያ ካሉ 108 የከረሜላ ፋብሪካዎች ውስጥ ከ2ቱ ውጪ ቀሪዎቹ ማለትም 95 በመቶ የሚሆኑት ከደረጃ በታች እንደሚያመርቱ ተገልጿል።
ወ/ሪት ህሊና እንዳሉት ከታዩት ዋና ዋና ክፍተቶች ከሚመረትበት ቦታ ፅዳት ጉድለት ባለፈ ምርቱ ከተመረተ በኋላ ገላጭ የሆነ የራሱን ማሸጊያ እንደሌላቸው ገልፀዋል።
በተያያዘም በየደረጃው ያሉ ተቆጣጣሪ አካላት የክትትል ክፍተትም ለዚህ እንደ አንድ ምክንያት መሆኑን ጠቁመው ከዚህ በኋላ እርምጃ መውሰድ እንደሚጀመር ተናግረዋል፡፡
ለዚህም የኢትዮጲያ ምግብ እና መድሃኒት ቁጥጥር ባለስልጣን መስርያ ቤት የአሰራር መመርያ እያዘጋጀ መሆኑንም ጠቁመዋል።
ከዛም በተጨማሪ ዛሬ የኢትዮጲያ ደረጃዎች ኤጀንሲ አዘጋጅቶት በነበረው ውይይት ላይ እንደተነሳው ከ2006 አስከ 2009 የተከፈቱ የከረሜላ ፋብሪካዎች ማለትም 40 የሚሆኑት ቀይ መስመር ውስጥ ናቸው ተብሏል።
በኢትዮጲያ 108 የከረሜላ አምራቾች ሲኖሮ ከ1987 አስከ 2005 ድረስ 80 የነበሩ ሲሆን ከ2006 አስከ 2009 ባለው መረጃ 40 መጨመራቸውን እና አሁን 108 እንዳሉ ተጠቁሟል፡፡
በረድኤት ገበየሁ
የካቲት 18 ቀን 2013 ዓ.ም











