ስፔን ሰዎች ራሳቸውን በተወሰነ ደረጃ ህይወታቸውን እንዲያጠፉ የሚፈቅደውን ህግ ስታፀድቅ አራተኛዋ የአውሮፓ ሀገር ናት፡፡
የማዕከላዊውና የግራ ዘመም ፓርቲዎች ህጉ እንዲጸድቅ ከፍተኛ ድጋፍ መስጠታቸዉም ታዉቋል፡፡
ከሰኔ ጀምሮ ተግባር ላይ መዋል ይጀምራል የተባለው ይህ ህግ በእድሜ አዋቂዎች ሆነው በማይድን በሽታ የሚሰቃዩ ህመምተኞች ፤ህመሙን መቋቋም የማይችሉ ከሆነ የራሳቸውን ህይወት ማጥፋት ምርጫው እንዳላቸው የሚፈቀድ ህግ ነው፡፡
ይህ ህግ ከመፅደቁ በፊት አንድን ሰው በእንደዚህ አይነት ሁኔታ እንዲሞት መርዳት በስፔን እስከ 10 አመት የሚያሳስር ወንጀል ነበር፡፡
ህጉ ከፀደቀ ከደቂቃዎች በኋላ የስፔኑ ጠቅላይ ሚኒስትር ፔድሮ ሳንቼዝ በትዊተር ገጻቸዉ ዛሬ ይበልጥ ሰብአዊ፣ ፍትሀዊ እና ነፃ ሀገር ሆነናል ሲሉ አስፍረዋል፡፡
በሰፊው በህብረተሰቡ ሲፈለግ የነበረው ይሄ ህግ ዛሬ እውን ሆኗል ሲሉ አክለዋል ይህ ህግ በወግ አጥባቂዎችና በሀይማኖተኞች ዘንድ ግን ከፍተኛ ውግዘት ደርሶበታል፡፡
ቤልጄም፣ ሉግዘምበርግ፣ ኔዘርላንድ፣ ካናዳ እና ኮሎምቢያ ይሄ ህግ ተግባራዊ የሆነባቸው ሀገራት ናቸው፡፡
በፖርቱጋል በዚህ ሳምንት በተመሳሳይ ፕርላማው ህግ አድርጎ ሊያፀድቀው የሞከረ ቢሆንም የሀገሪቱ ከፍተኛው ፍርድ ቤት ኢ-ህገ መንግስታዊ ሲል ውድቅ አድርጎታል፡፡
ቢቢሲ
በሄኖክ አስራት
መጋቢት 10 ቀን 2013 ዓ.ም











