አዉደ ርዕዩ እስከ ሚያዝያ 10/ 2013 ድረስ የሚቆይ ሲሆን ”አርቴፊሻል ኢንተሊጀንስ ለሁሉም” በሚል መሪ ቃል ነዉ በኢንተርኮንቲኔንታል ሆቴል በመካሄድ ላይ የሚገኘዉ፡፡
አርቴፊሻል ኢንተሊጀንስ የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ ወደ ዲጂታላዊ አሰራር በማሸጋገር ኢትዮጵያን መካከለኛ ገቢ ካላቸው ሀገራት ተርታ ለማሰለፍ ራዕይ አንግቦ እየሰራ መሆኑም በዚሁ ወቅት ተነግሯል፡፡
አርቴፊሻል ኢንተሊጀንስ ሲባል ማሽኖች በሰው ሰራሽ መንገድ የማሰብ ክህሎትን በመጠቀም ወይም የሰው ልጆችን የአዕምሮ ችሎታ የሚያስመስል የምህንድስናና የስልተ-ቀመር (Algorithm) ሳይንስ ውጤት እንደሆነ ነው የአርቴፊሻል ኢንተሊጀንስ ማዕከል የገለፀው።
እንደነዚህ አይነት ማሽኖች የሰው ልጅን በማገዝ በተለያዩ የስራ መስኮች እንዲሰማሩ፣ ከዚህ አለፍ ሲልም ሙሉ በሙሉ እራሳቸውን ችለው ያለማንም የሰው ልጅ እርዳታ የእለት ተእለት እንቅስቃሲያቸውን በራሳቸው መስራት የሚችሉ እንደማለት መሆኑንም እንዲሁ ማእከሉ አብራርቷል።
የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚንስትሩ ዶክተር አብርሃ በላይ እንደተናገሩት፣ የአርቴፊሺያል ኢንተሊጀንስ ዘርፍ ኢትዮጵያ መካከኛ ገቢ ካላቸው ሀገራት ተርታ ለማሰለፍ የምታደርገውን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ትራንስፎርሜሽን እውን ለማድረግ ያግዛታል ብለዋል።
በተጨማሪም እንደሀገር የዲጂታል ኢኮኖሚን ለመገንባትና በሌሎች ኢኮኖሚያዊ ዘርፎች ላይ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ራዕይና ተልዕኮ አንግቦ በመስራት ላይ እንደሚገኝም ተናግረዋል።
ዛሬን ጨምሮ ለቃጣዮቹ 4 ቀናት በዘርፉ የተሰሩ ስራዎችን፣ ያለበት እድገት፣ ችግሮችና ዘርፉን ለማሳደግ የሚያስችሉ ምክክሮች እንደሚደረጉ ሚንስትሩ ዶ/ር አብርሃም በላይ ተናግረዋል፡፡
በጅብሪል ሙሃመድ
ሚያዝያ 07 ቀን 2013 ዓ.ም











