በንግድ ቤቶች በሆቴል ቤቶች እና ሰው በሚሰበሰብባቸው ቦታዎች አካባቢ ለቱሪስት ሲጋራ የሚያስጨሱ ተቋማት እና ግለሰቦች ከድርጊታቸው እንዲቆጠቡ ባለስልጣን መስሪያ ቤቱ ጠይቋል፡፡
በአዲስ አበባ ከተማ በተለያዩ ስፍራዎች የውጭ ሀገር ዜጎች እንደፈለጉ ሲጋራ እያጨሱ እንደሆነ ይታያል፡፡
በከተማዋ የሚገኙ የንግድ ተቋማት በተለይም ሆቴሎች፣ ቱሪስቶች ሲጋራ እንዲያጨሱ ፍቃድ እንደሚሰጡ ተነግሯል፡፡
ይህንንም ተከትሎ የንግድ ቤቶቹ የትንባሆ ምርት ለመከላከል እና ለመቆጣጠር የወጣውን መመርያ እየጣሱ ይገኛሉ ሲል የምግብ እና የመድሀኒት ቁጥጥር ባለስልጣን አስታዉቋል፡፡
የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ወ/ት ሄራን ገርባ እንደተናገሩት የውጭ ዜጋ ተብሎ ህጉ የሚጣስበት ምክንያት የለም፤ተቋማት ይህንን ተግባራዊ ማድረግ አለባቸው ብለዋል፡፡
ይህንን መመርያ ጥሰው በሚገኙ ተቋማት እና ግለሰቦች ላይ ህጋዊ እርምጃ እንደሚወሰድባቸው ነው ዳይሬክተሯ ያረጋገጡት፡፡
ገቢ ለማግኘት በሚል መመርያውን ተግባራዊ የማያደርጉ የንግድ ተቋማት እና ግለሰቦች ከዚህ ድርጊታቸዉ ተቆጥበዉ ሀላፊነታቸው በአግባቡ መወጣት እንዳለባቸዉም አሳስበዋል፡፡
ውድ አድማጮቻችን እና ተከታዮቻችን የኢትዮ ኤፍ ኤም ስርጭቶችን፣ዜናዎችን እና ሌሎች ዝግጅቶችን ለመከታተል የቴሌግራም ቻናላችንን https://t.me/ethiofm107dot8 ይቀላቀሉ።
በሔኖክ ወ/ገብርኤል
ሰኔ 01 ቀን 2013 ዓ.ም











