ከአራት ዓመታት በፊት የኤርፖርቶች ድርጅት የሚዛን አማን አውሮፕላን ማረፊያ ለመገንባት ጥናት መካሄዱ እና የዲዛይን ስራ የተጠናቀቀለት የአውሮፕላን ማረፊያው ፣ለግንባታ የሚሆነውም የገንዘብ መጠን በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ጸድቆ ወደ ጨረታ መገባቱ ይታወሳል፡፡
የቤንች ሸኮ አስተዳደርም ከ21.9 ሚሊዬን ብር በላይ ለህብረተሰቡ ካሳ በመክፈልና ቦታውን ከይገባኛል ነጻ በማድረግ ሰዎችን መልሶ የማስፈር ስራ እንደሰራም ነው ያስታወቀው፡፡
ለአውሮፕላን ማረፊያ ቦታ እንዲሆን በዞኑ በኩል ከ100 በላይ አባወራዎችን ቦታቸው እንዲለቁ ተደርጓል፡፡
በዚህ መሀል የኤርፖርቶች ድርጅት ከዚህ በፊት ተሰጥቶ የነበረው የግንባታ ቦታ እንዲለወጥለት መጠየቁ አግባብነት የሌለው ነገር ነው ሲል ዞኑ ያስታወቀው፡፡
የቤንች ሸኮ ዞን አስተዳደር አቶ ፍቅሬ አማን ለኢትዮ ኤፍ ኤም እንደተናገሩት የኤርፖርቶች ድርጅት የዞኑን አቅም የማይመጥን ስራ እየሰራ ነው ብለዋል፡፡
የቤንች ሸኮ ዞን አስተዳደር የኤርፖርቶች ድርጅት ለዞኑ ነዋሪዎች ይቅርታ መጠየቅ አለበት ሲል አስታውቋል፡፡
አውሮፕላን ማረፊያ እንዲሰራ እምነታችንና ባህላችንን ወደ ጎን በመተው መካነ መቃብር ብናስነሳም እስካሁን ሊሰራ ባለመቻሉ በህብረተሰቡ ዘንድ ትልቅ ቅሬታ እንዲነሳ አድርጓል ተብሏል፡፡
ህብረተሰባችንንና ያለንን ዕምቅ አቅም በማይመጥን መንገድ ተለዋጭ ቦታ እንዲዘጋጅ መጠየቁ ተገቢነት የሌለውና ክብራችንን የሚጎዳ ተግባር ነው የተፈጸመው ብለዋል፡፡
ድርጅቱ ያደረገው ነገር ህዝባችንን አሳንሶ ማየት ስለሆነ ይህንን ስህተት የሰራው አካል ህዝባችንን ይቅርታ እንዲጠይቅና ግንባታው በፍጥነት እንዲጀመር እናሳስባለን ሲሉ ተናግረዋል፡፡
ውድ አድማጮቻችን እና ተከታዮቻችን የኢትዮ ኤፍ ኤም ስርጭቶችን፣ዜናዎችን እና ሌሎች ዝግጅቶችን ለመከታተል የቴሌግራም ቻናላችንን https://t.me/ethiofm107dot8 ይቀላቀሉ።
በሔኖክ ወ/ገብርኤል
ሰኔ 01 ቀን 2013 ዓ.ም











