በኢትዮጵያ ቱርክ አምባሳደር ያፕራክ አልፕ እንዳስታወቁት፤በአሁኑ ሰዓት ምንም አይነት የቱርክ ሰዉ አልባ አዉሮፕላን ወይንም ድሮኖች በኢትዮጵያ የሉም ብለዋል፡፡
የቱርክ መንግስት ለኢትዮጵያ ድሮኖችን ድጋፍ እያደረገ ነዉ በሚል በማህበራዊ ሚዲያ የሚናፈሰዉ ወሬ ከእዉነት የራቀ ስለመሆኑም አምባሳደሯ አንስተዋል፡፡
ቱርክና ኢትዮጵያ ሽብርተኝነትን በመዋጋት ረገድም ተቀናጅዉ እንደሚሰሩ የገለፁት ያፕራክ፤በተለይም እንደ ፌቱላህ አይነት ተስፋፊ የሽብር ቡድኖችን በጋራ ማስወገድ ይገባል ብለዋል፡፡
ሁለቱ አገራት በፖለቲካና በኢኮኖሚ ያላቸዉን ግንኙነት ለማሳደግ እንደሚሰሩም በመግለፅ በቀጣይም የንግድ ግንኙነቱን ማጠንከር ይገባል ማለታቸዉን አናዶሉ ኤጀንሲ ነዉ የዘገበዉ፡፡
አሁን ላይ ከ2መቶ 20 በላይ የቱርክ ኩባንያዎች በኢትዮጵያ እንደሚገኙና ከ2.5 ቢሊዮን ዶላር ኢንቨስት ማድረጋቸዉን ያስታወቁት አምባሳደር አልፕ ለ25 ሺህ ዜጎች የስራ እድል እንደተፈጠሩም ገልፀዋል፡፡
ከዚህ ባለፈም በትምህርት ዘርፍ በ የአመቱ ለ75 ኢትጵያዉያን የትምህርት ዕድል እንደምትሰጥም ተጠቁሟል፡፡
ባጠቃላይ የቱርክ መንግስት በኢንቨስትመንት፤ በቴክኖሎጂ ልዉዉጥ፤ በሰብአዊ እርዳታ በቱሪዝምና በሌሎችም ዘርፎች ከኢትዮጵያ ጋር በቅርበት እንደሚሰራ ተነግሯል፡፡
አባቱ መረቀ
ሐምሌ 09 ቀን 2013 ዓ.ም











