በሆስፒታሉ የቀዶ ህክምና ክፍል ባለሙያዎች እንደነገሩን በውሀ እና በህክምና መሳሪያዎች በየጊዜው መበላሸት ምክንያት ብዙ ታካሚዎች የቀዶ ህክምና ቀጠሮአቸው እንደሚሰረዝ ገልጸዋል።
በአለም ጤና ድርጅት ከተቀመጠው የ5 በመቶ ስረዛ በላይ ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል በዚህ አመት ብቻ እስከ 19 በመቶ የቀዶ ህክምና ቀጠሮ መሰረዙንም ሰምተናል።
የላውንደሪ ማድረቂያው አለመስራትና ለህክምና የሚያስፈልጉ ልብሶች ለመድረቅ ጊዜ መውሰድም አንዱ ቀዶ ህክምናውን ከሚያዘገዩ ምክንያቶች ይጠቀሳሉ።
የቀዶ ህክምና መሰረዝ ደግሞ የወረፋ መጠበቂያ ዝርዝሩን ይጨምራል፤ በዚህም በአሁኑ ሰአት እስከ 3ሺ ታካሚዎች ወረፋ ሊጠብቁ ችለዋል ብለውናል የቀዶ ህክምና ክፍል ባለሙያዎቹ።
ችግሩ መች መፍትሄ ያገኛል ያልናቸው የአዲስ አበባ ጤና ሳይንስ ኮሌጅ የህዝብ ግንኙነትና ኮሚኒኬሽን ኤክስፐርት አቶ ተስፋዬ ሰለሞን የሆስፒታሉ ማኔጅመንት አይቶታል ችግሩ አሁን ካሉን ባዮሜዲካል ኢንጅነሮች በላይ ስለሆነ ሌሎች ልምድ ያላቸው ባለሙያዎችን ለማሰራት እየተዘጋጀን ነው ሲሉ ለጣቢያችን ምላሽ ሰጥተዋል።
ውድ አድማጮቻችን እና ተከታዮቻችን የኢትዮ ኤፍ ኤም ስርጭቶችን ቻናላችንን እና ሌሎች ዝግጅቶችን ለመከታተል የቴሌግራም ቻናላችንን https://t.me/ethiofm107dot8 ይቀላቀሉ።
መቅደላዊት ደረጄ
ነሐሴ 25 ቀን 2013 ዓ.ም











