በተለያዩ የልዩ ወረዳው አካባቢዎች እየተከሰተ ያለው የተምች ወረርሽኝ በባለሙያዎች ዳሰሳ መረጋገጡን የአማሮ ልዩ ወረዳ የግብርና ፅ/ቤት ም/ሀላፊና የእርሻ ዘርፍ አስተባባሪ አቶ ከፍያለው አዱላ ለኤትዩ ኤፍ ኤም ተናረዋል፡፡
በተለይ በስድስት ቀበሌዎች ማለትም በቡኒት፣ በመዳይኔ፣ በዳይኬታና ወርካለ – ቦንጮ፣ በከሬዳ ተምቹ መከሰቱን ነግረውናል ፡፡
ለዚህ የተምች መከሰት ዋና ምክንያት በተያዘው በልግ ወቅት እየጣለ ያለው ዝናብ በመጠንም ሆነ በሥርጭት ያልተስተካከለ ከመሆኑ የተነሳ ለተለያዩ ተባዮችና ነፍሳት መከሰት ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን እንደሆነ ም/ሀላፊ አቶ ከፍያለው አመላክቷል።
ተምቹ የመዛመት እድሉ ከፍተኛ በመሆኑ በሁሉም ቀበሌዎች የአሰሳና ቅኝት ሥራዎችን በማካሄድ የመከላከልና የመቆጣጠር ተግባራት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልፀው፣ አርሶ አደሮችና አርብቶ አደሮች በመከላከል ዙሪያ ትኩረት እንዲሰጡም ጠይቀዋል፡፡
ከማሣ ውጭ እየተሳበ ስለሚመጣ ወደ ማሣ ሳይገባና ከአንዱ ማሣ ወደ ሌላ ሳይደርስ 50 ሣንቲ ሜትር ጥልቀትና ስፋት ያለ ቦይ በመቆፈር ተምቹን ህብረተሰቡ መከላከል እንዳለበት አቶ ከፍያለው አሳስበዋል።
ተምቹን ባለበት ለማቁም እና እንዳይዘመት ለማድረግ ጸረ- ተባይ መድሀኒቱ ወደ ወረዳ ማዕከል ደርሷል ብለዋል።
ከአቅም በላይ የሚሆን ከሆነ በፍጥነት ጸረ-ተባይ ኬሚካል በመርጨት ችግሩን መቆጣጠርና መከላከል እንደሚቻል የገለፁት ም/ሀላፊ፣ ካለው የጎንዮሽ ጉዳት አንጻር የኬሚካል ርጭቱ ግን የመጨረሻ አማራጭ መሆኑን አስረድተዋል።
ያይኔአበባ ሻምበል
ግንቦት 22 ቀን 2014 ዓ.ም