በከፍታኛ ሁኔታ በቀጠለው የነዳጅ ሰልፍ ምክንያት፣ በተለያዩ አካባቢዎች የህዝብ ማመላለሻ ዘርፉ ላይ ከፍተኛ መስተጓጉሎች እየታዩ ይገኛሉ፡፡
በመሆኑም ይህንን ችግር ከግምት ዉስጥ በማስገባት የኢትዮጲያ ነዳጅ ማደያዎች ማህበር የህዝብ ማመላለሻ ተሸከርካሪዎች ( ታክሲዎችና ሃይገሮች) ቅድሚያ ተሰጥቷቸው ነዳጅ እንዲያገኙ ለማድረግ ዝግጁ መሆኑን አስታውቋል፡፡
ማህበሩ እየተስተዋለ ያለው የህዝቡ መጉላላት አሳስቦኛል ያለ ሲሆን፣ ያለውን ረጃጅም የትራንስፖርት ሰልፎች ፋታ ለመስጠት እና የህዝብ ትራንስፖርት ችግሩን ለማቃለል ይህንን መላ መዘየዱን ነግሮናል፡፡
በየማደያዎቻችን አሁንም የተሸከርካሪ ሰልፎች እንደቀጠሉ ናቸው ያሉን የማህበሩ ቦርድ አባል አቶ ደሳለኝ አበባየሁ፣ የህዝብን እንግልት ለመቀነስ በማሰብ ማህበሩ ይህንን ለመተግበር መወሰኑን ገልጸውልናል፡፡
አቶ ደሳለኝ አበባየሁ ይህ እቅድ የህዝቡን ችግር የሚፈታ በመሆኑም የመንግስትን እና የፖሊስን ድጋፍ ካገገኘን በየማደያዎቹ አሰራሩ ይተገበራል ሲሉ ነግረውናል፡፡
የኢትዮጵያ ነዳጅ ማደያዎች ማህበር አሁን ካለው የነዳጅ ችግር ጋር በተያያዘ ከሌሎች ዘርፎች በበለጠ ለህብረተሰቡ ትኩረት መሰጠት እንደሚገባው በማመን ያቀረበዉ ምክረሃሳብ መሆኑን ገልጿል፡፡
አሽከርካሪዎች እና የመንግስት አካላት ይህንኑ እንዲረዱም ጠይቋል፡፡
በአብዱሰላም አንሳር
ሰኔ 24 ቀን 2014 ዓ.ም











