የሩሲያዉ ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን ከማሊ መሪ አስሚ ጎይታ ጋር በምግብ፣ ነዳጅ እና ማዳበሪያ አቅርቦት ዙሪያ በስልክ መወያየታቸዉን ክሬምሊን አስታዉቋል፡፡
አስሚ ጎይታ በትዊተር ገጻቸዉ ላይ ሩሲያ ለማሊ መንግስት ፖለቲካዊ የሽግግር ሂደት ድጋፍ እንደምታደርግ መነጋገራቸዉን አስፍረዋል፡፡
‹‹የሩሲያ ፌዴሬሽን ለማሊ መንግስት ፖለቲካዊ ሽግግር ስለሚያደርገዉ ድጋፍ ተነጋግረናል ብለዋል አስሚ ጎይታ፡፡
የማሊን ሉዓላዊነት እና የህዝቧን ፍላጎት የሚያከብረዉን ግንኙነታችንንም በእጅጉ እንደማደንቀዉ ገልጨላቸዋል›› ሲሉ በትዊተር ገጻቸዉ ላይ አስፍረዋል፡፡
የማሊ ወታደራዊ ሀይል በመፈንቅለ መንግስት ከሁለት ዓመት በፊት ወደ ስልጣን የመጣ ሲሆን ከጎረቤት እና ሌሎች የምዕራብ አፍሪካ ሀገራት ጋር በምርጫ ጊዜ መራዘም እና ኢስላማዊ ሀይሎችን ለመዋጋት የሩሲያ ቅጥረኛ ወታደሮችን በመጠቀሙ ብዙ ጊዜ ግጭት ዉስጥም ገብቷል፡፡
የምዕራብ አፍካዊቷ ሀገር ማሊ ከረጅም ጊዜ አጋሯ እና የቀድሞ ቅኝ ገዢዋ ፈረንሳይ ጋር ያላት ግንኙነት በመሻከሩ በሶቪየት ዘመን የነበረዉን የሩሲያ ማሊ ግንኙነት አጠናክራ መቀጠሏን የሮይተርስ ዘገባ ያመለክታል፡፡
በእስከዳር ግርማ
ነሐሴ 05 ቀን 2014 ዓ.ም











