የትምህርት ሚኒስቴር የ2014ዓ.ም የ12ኛ ክፍል ፈተና ውጤት ከወር ባነሰ ጊዜ እንደሚገለጽ አስታውቋል፡፡
በ2014 ዓ.ም ሀገር አቀፍ ፈተና በአጠቃላይ ከ900 ሺህ በላይ ተፈታኞች ፈተናውን የወሰዱ ሲሆን ይህም ከዚህ ቀደም ከነበረው የተፈታኝ ቁጥር በእጅጉ እንደሚልቅ ተገልጿል።
በአጠቃላይም ከተመዘገቡት ተማሪዎች ውስጥ 98.8 በመቶ ተማሪዎች ፈተናዉን ወስደዋል፡፡
ፈተናውን ለማስፈፀምም ከ25 ሺህ በላይ ፈተና አስፈፃሚዎች እና ከ 6 ሺህ በላይ የፀጥታ ሀይሎች ለፈተናው ተሰማርተዉ እንደነበር ተነግሯል፡፡
በሀዋሳ ዩኒቨርስቲ ያጋጠመው አደጋ እና ባህር ዳር ዩኒቨርስቲ ተፈታኞች ያጋጠመዉ ትራፊክ አደጋ ፣ በመቅደላ አምባ፣ ደብረማርቆስ፣ ባህር ዳር እና ደብረታቦር ዩኒቨርስቲዎች ላይ 12 ሺ 993 ተማሪዎች አንፈተንም ብለው ፈተና ትተው መውጣታቸው በፈተና ወቅት ያጋጠሙ ክስተቶች መሆናቸውን ሚኒስትሩ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ አስታዉሰዋል።
በፈተና ወቅትም በ33 የፈተና ጣቢያዎች 53 ተፈታኞች ስልክ ይዘው ለመግባት የሞከሩ ሲሆን ፈተና አስፈፃሚዎችንም የማዋከብ እና ሌሎች የፈተና ስነ-ምግባር ግድፈቶች መታየታቸውን እና በፈታኞችም በኩል የፈተና ስርዓትን ያለመከተል ችግሮች እንደነበሩም ተገልጿል።
በሔኖክ ወ/ገብርኤል
ጥቅምት 16 ቀን 2015 ዓ.ም











