በአዲስ አበባ ከተማ በሁሉም ክ/ከተሞች በሚገኙ ትምህርት ቤቶች ውጤታማ የሆኑ አካል ጉዳተኛ ተማሪዎች የሚሸለሙበት ፕሮግራም በዛሬው እለት ይካሄዳል ተብሏል፡፡
ህዳር 19 በብሔራዊ ቲያትር እንችላለን 3 አለም አቀፍ የአካል ጉዳተኞችን ቀን በማስመልከት ካቲም ዲሴቢሊቲ ዳንስ ኤንድ ኪነጥበብ፤ ከኢትዮጵያ አካል ጉዳተኞች ማህበራት ፌዴሬሽን ጋር በጋራ በመሆን ባዘጋጀው ፕሮግራም ከአስራ አንዱም ክፍለ ከተሞች ውጤታማ የሆኑ አካል ጉዳተኛ ተማሪዎች እንደሚሸለሙ የካቲም ዲሴቢሊቲ ዳንስ እና ኪጥበብ ዳሬክተር አቶ አማኑኤል ሰለሞን ለኢትዮ ኤፍኤም ተናግረዋል፡፡
በፕሮግራሙ ረዥም ዓመት በመምህርነት ያለገሉና እያለገሉ የሚገኙ አካል ጉዳተኛ መምህራንም የእውቅና ሽልማት እንደሚሰጣቸው ሰምተናል፡፡
በእለቱ በሚኖረው ዝግጅትም ውጤታማ የሆኑ አካል ጉዳተኛ ተማሪዎች ለሌሎች አካል ጉዳተኛ ተማሪዎች ልምዶቻቸው እንደሚያካፍሉ ይደረጋል፡፡
በተጨማሪም ታዳሚያን ከብሔራዊ ቲያትር በር አንስቶ እስከ መቀመጫ ወንበራቸው ድረስ በክራንች እና በዊልቸር እንዲገቡ የታሰበ ሲሆን የተለያየ ምርት የሚያመርቱ አካል ጉዳተኛ አምራቾች ምርታቸውን የማሳየትና የመሸጥ እድልም እንደተመቻቸላቸው አቶ አማኑኤል ነግረውናል፡፡
ለትርፍ ያልተቋቋመው ካቲም ዲሴቢሊቲ ዳንስ እና ጥበብ ከኢትዮጲያ አካል ጉዳተኞች ማህበራት ፌዴሬሽን ጋር በመሆን ባዘጋጀው በዚህ ፕሮግራም የኪነ-ጥበብ ባለሙያዎች፤ ከፍተኛ የመንግስት ሃላፊዎችና ተጋባዥ እንግዶች እንደሚታደሙበት አቶ አቤኔዘር ነግረውናል፡፡
ሃገር ኣቀፍ የአካል ጉዳተኞች ቀን ህዳር 24 በድሬዳዋ ከተማ ይከበራል፡፡
በየውልሰው ገዝሙ
ህዳር 19 ቀን 2015 ዓ.ም











