ወጂዝ ኢንጅነሪንግ ኃ/የተ/የግ/ማህበር ከ2010 ጀምሮ ቤት የሚፈልጉ ግለሰቦችን በ20 ወራት ውስጥ ቤት ሰርቶ እንደሚያስረክብ በመግለፅ በተያዘው ጊዜ ውስጥ ገንዘቡን ከፍለው እንዲጨርሱ አድርጓል።
ግለሰቦቹ ገንዘቡን በተባለው ጊዜ እንዲሁም ቀደም ብለው ከፍለው ቢጨርሱም ቤቱን መረከብ እንዳልቻሉ ይገልፃሉ።
የ2010 ተመዝጋቢዎች በሳይት “ሲ” እና “ዲ” ተከፍሎ ቤታቸው እየተገነባ እንደሆነ ቢነገራቸውም፣ በሳይት “ሲ” ያለው የግንባታ ደረጃ ከ35 በመቶ እንደማይበልጥ እና የሳይቲ “ዲ” ግንባታ ደግሞ ወደ 50 በመቶ እንደደረሰ ተናግረዋል።
በውላቸው መሠረት በ 2 ዓመት ጊዜ ቤታቸውን እንደሚረከቡ የተገለፀላቸው የቤት ባለቤቶች፣ 5 ዓመት መጠበቃቸውን እና ቤቱን ማግኘት አለመቻላቸውን በቅሬታ አንስተዋል።
ቤቱን ለግለሰቦቹ ከማስረከብ ይልቅ ያላለቀውን የቤት ግንባታ በማስያዝ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እና ከአዋሽ ባንክ 800 ሚሊየን ብር መበደሩን ለማወቅ ተችሏል።
ግለሰቦቹ ቤታቸውን ማግኘት ባይችሉ እንኳን የከፈሉት ገንዘብ እንዲመለስላቸው ቢጠይቁም፣ ለቤቱ ከከፈሉት ከ2 ሚሊየን ብር በላይ ተጨማሪ ሌላ 4 ሚሊየን ብር በ3 ቀናት ውስጥ እንዲከፍሉ እና ድርጅቱ በ12 ወራት ውስጥ ቤቱን አጠናቆ እንደሚያስረክባቸው በመግለፅ ይህ ካልሆነ ግን ድርጅቱ ጉዳዩን ወደሚፈታው የህግ አካል ለመሄድ እንደሚገደድ መግለጹን ተናግረዋል።
እኛው ተበድለን እያለ እንደበደለ ሰው ተቆጥረን ይህ መሆኑ ትክክል አይደለም የሚሉት ቅሬታ አቅራቢዎቹ የሚመለከተው አካል መፍትሔ እንዲሰጣቸውም ጠይቀዋል፡፡
አሁንም ቢሆን የምንፈልገው የከፈልንበትን ቤታችንን ነው ሲሉ አፅንኦት ሰጥተው ተናግረዋል።
የቤት አልሚውን ምላሽ ለማካተት ያደረግነው ጥረት አልተሳካም፡፡
በእስከዳር ግርማ
ታህሳስ 21 ቀን 2015 ዓ.ም











