ላለፉት ስምንት ቀናት በእስር ላይ የቆዩት አራት የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ጉባኤ (ኢሰመጉ) ሰራተኞች፤ የገንዘብ ዋስትና በማስያዝ ከእስር እንዲለቀቁ በፍርድ ቤት ተወሰነላቸው።
በኦሮሚያ ክልል የሰበታ ከተማ ወረዳ ፍርድ ቤት ዋስትናውን የፈቀደው፤ ዐቃቤ ህግ የሰራተኞቹን በዋስ መውጣት እንደማይቃወም በመግለጹ ነው ተብሏል።
ፍርድ ቤቱ የኢሰመጉን ሰራተኞች ጉዳይ የተመለከተለው፤ ትላንት በዋለው ችሎት ፖሊስ የጠየቀው ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ ውድቅ ከተደረገ በኋላ በአዲስ መዝገብ አቤቱታ በማቅረቡ ነዉ ተብሏል፡፡
የኢሰመጉ ሰራተኞች በጠበቃቸው በኩል ትላንት ከሰዓት በኋላ ያቀረቡት አቤቱታ የዋስትና መብታቸው እንዲከበርላቸው የሚጠይቅ ነበር።
ይህንን አቤቱታ ዛሬ ሐሙስ ጥር 4 ረፋዱን የተመለከተው የሰበታ ከተማ ወረዳ ፍርድ ቤት፤ ዐቃቤ ህግ በአቤቱታው ላይ ያለውን አስተያየት እንዲሰጥ መጠየቁን የሰራተኞቹ ጠበቃ አዲሱ አሸናፊ ለ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” ተናግረዋል።
አስተያየት የተጠየቀው አቃቤ ህግም “ምርመራውን ስለጨረስን እና የዋስ መብት የማያስከለክል ስለሆነ በዋስ ቢወጡ አንቃወምም” የሚል ምላሽ መስጠቱን ጠበቃው አስረድተዋል።
ይህንን ተከትሎም ፍርድ ቤቱ የኢሰመጉን ሰራተኞች “ደመወዝ እና ኢኮኖሚያዊ አቅም” በግምት ውስጥ ባስገባ መልኩ የገንዘብ ዋስትና መፍቀዱን አስታውቀዋል።
ኢትዮ ኤፍ ኤም 107.8 የኢትዮጵያዊያን
ጥር 04 ቀን 2015 ዓ.ም











