ኢትዮ ቴሌኮም ከአገልግሎት ሰጪ አጋሮቹ ጋር በመተባበር አዳዲስ የዲጂታል መዝናኛ አገልግሎቶችን ይፋ አድርጓል ።
ኩባንያው አራት አዳዲስ አገልግሎቶችን ይዞ መምጣቱን የገለፁት የኩባንያው ዋና የማርኬቲንግ ኦፊሰር የሆኑት አቶ ሰኢድ አርጋው ናቸው።
በዛሬው ዕለት ይፋ ከተደረጉት አገልግሎቶች መካከል በሐበሻ ቪው የሚቀርበው የቪዲዮ ስትሪሚንግ አንዱ ሲሆን፣ ደንበኞች የቀጥታ የቴሌቪዥን ፕሮግራሞችን ፣ ድራማዎችን ፣ ፊልሞችን እና ሌሎች የተመረጡ አገልግሎቶችን ኢንተርኔትን በመጠቀም በሞባይል ስልካቸው፣ በቴሌቭዥናቸው እንዲሁም በኮምፒውተር ላይ መመልከት ይችላሉ።
ለ 1 ወር ያህል በነፃ አገልግሎቱን መጠቀም የሚቻል ሲሆን በወር ከ 150 እስከ 300 ብር በመክፈል መጠቀም ይቻላል ተብሏል።
ሁለተኛው የመዝናኛው ዘርፍ የዲጂታል አገልግሎት የሚሰጠው ሰዋሰው የሙዚቃ መተግበሪያ ሲሆን የሃገር ውስጥ እና የውጪ ሙዚቃዎችን በአንድ ቦታ የሚያገኙበት እና የሚያደምጡበት አማራጭ ነው። አገልግሎቱንም በቴሌብር ሱፐርአፕ መተግበሪያ ፣ በሰዋሰው ድህረገፅ ላይ ማግኘት ይቻላል።
ሌላው በዛሬው ዕለት ይፋ የተደረጉት ቴሌጌም እና ቴሌዊን የተሰኙ የሞባይል ጌሞች በቴክኖላብ ኃ.የተ.የግ.ማ እና አይኮኔክት ዲጂታል ሰርቪስ የቀረቡ ሲሆን፣ ቴሌጌም አዋቂዎችም ሆኑ ታዳጊ ልጆች የተመረጡ 500 የሞባይል ጌሞችን በአነስተኛ ክፍያ ያለገደብ እንዳያወርዱ እና ያለ ጣልቃ ገብ ማስታወቂያዎች እንዲጫወቱ ያስችላቸዋል ተብሏል።
ይህን የጌም አገልግሎት 2ቀን በነፃ መጠቀም የሚቻል ሲሆን በቀን 3 ብር በመክፈል ደግሞ አገልግሎቱን ማግኘት ይቻላል።
በተጨማሪም ደግሞ ደንበኞች በአይኮኔክት የቀረቡትን የቴሌዊን ጌሞችን በቴሌዊን ድረገፅ ወይም በአጭር የፅሁፍ መልዕክት ወደ *985# በመደወል ዕለታዊ ወይም ሳምንታዊ ጥቅሎችን መመዝገብ እና መጫወት እንደሚችሉ ተገልጿል ። ጌሞቹ በጥንቃቄ የተመረጡ እና ሁሉንም የእድሜ ክፍል ያማከሉ መሆናቸው ነው አቶ ሰኢድ ገልፀዋል ።
በእስከዳር ግርማ
ሚያዝያ 26 ቀን 2015 ዓ.ም











