በፖለቲካ አመለካከታችን ብቻ ከቤተሰቦቻችን እንዳንገናኝ ተደርገናል ሲሉ የቁጫ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ቁሕዴፓ) አመራሮች ለኢትዮ ኤፍ ኤም ተናግረዋል።
የፓርቲው ዋና ፀሃፊ አቶ በቀለ አበራ በአሁን ሰዓት የፓርቲው አባላት ቤተሰቦቻቸው በከባድ ሁኔታ ውስጥ እንደሚገኙ ነው የገለጹት።
የፖርቲው አባል በመሆናችን እና የማንነት ጥያቄ በማቅረባችን ብቻ የግድያ ሙከራ ተደርጎብን ከቁጫ ከተማ ለቀን ከወጣን ቆይተናል ብለዋል።
ከቤተሰቦቻቸው ጋር ከተለያዩ አንድ አመት ሊሞላቸው እንደሆነ የተናገሩት አቶ በቀለ፣ በከተማው ቤተሰቦቻቸው ለእስር እየተዳረጉ መሆናቸውን ገልጸዋል።
የፓርቲው ደጋፊ የሆኑ ግለሰቦች አሁንም ድረስ የንግድ ተቋሞቻቸው ተዘግተዋል፤በእርሻ መሬቶቻቸው እንዳይሰሩ ተደርገዋል እንዲሁም ተማሪዎች ትምህርት አቋርጠው ቆይተዋል ነው ያሉት።
በቁጫ ከተማ እየተደረገ ያለው ህገ-ወጥ ዘመቻ፣ዴሞክራሲያዊ መብታቸውን የጠየቀ ህዝብ ጥያቄ ማዳፈን መሆኑን ሃላፊው አንስተዋል።
በጉዳዩ ላይ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን(ኢሰማኮ) ተደጋጋሚ መግለጫዎችን ቢያወጣም መንግስት ግን ከቁብ እንዳልቆጠረው ፓርቲው ገልጿል።
በመሳይ ገ/መድህን
ሰኔ 20 ቀን 2015 ዓ.ም











