ክልሉ በህዝብ ተወካዮችም ሆነ በፌዴሬሽን ምክር ቤት ተወካይ በማጣቱ የተነሳ ለከፍተኛ ችግር መጋለጡን ነው የኢትዮጵያ ህዝብ እምባ ጠባቂ ተቋም የመቀሌ ቅርንጫፍ ለኢትዮ ኤፍ ኤም ያስታወቀው፡፡
የፌደራሉም ሆነ የክልሉ ግዚያዊ አስተዳደር የትግራይን ህዝብ ችግር መፍታት አልቻሉም ሲሉ የቅርጫፍ ጽሕፈት ቤት ሀላፊው አቶ ፀጋዬ እምባዬ ለኢትዮ ኤፍ ኤም ተናግረዋል፡፡
የትግራይ ህዝብ መጠነ ሰፊ ችግሮችን እየተጋፈጠ ነው፣ነገር ግን ችግሩን የሚያደርስለት አንድ ተወካይ እንኳ የለውም ብለዋል፡፡
በአሁን ሰዓት ህዝቡ በድሮንና በመድፍ እየሞተ ላይሆን ይችላል፣ ነገር ግን ግዜ በማይሰጠው ርሃብ እየሞተ ነው ሲሉ ለጣብያችን ተናግረዋል፡፡
አፋጣኝ የሆነ በህዝብ ተወካዮችም ሆነ በፌዴሬሽን ምክር ቤት ግዚያዊ ተወካይም ቢሆን ተወክሎ የክልሉን ችግር የሚያደርስ አካል ያስፈልገዋል ብለዋል፡
በትግራይ ክልል ለሁለት ዓመት ከቆየው ጦርነት በኃላ በርካታ ተፈናቃዮች እና ነዋሪዎች ለከፋ የምግብ አቅርቦት ችግር መጋለጣቸው ሲገለፅ መቆየቱ ይታወሳል፡፡
የዓለም አቀፍ ረጂ ተቋማት ከስርቆት ጋር በተያያዘ በክልሉ ያለውን የምግብ እርዳታ ካቋረጡት በርካታ ወራትን አስቆጥሯል ብለዋል፡፡
በአቤል ደጀኔ
ሕዳር 06 ቀን 2016 ዓ.ም











