በጉራጌ ዞን ለሁለተኛ ጊዜ ሚስቱን የገደለው ተከሳሽ የሞት ፍርድ ተፈረደበት።

የዞኑ ኮሙንኬሽን እንዳስታወቀው ድርጊቱ ፈፃሚ አቶ በሀሩ ወንድም አገኝ ጉባሞ በጉራጌ ዞን እኖር ኤነረ ወረዳ የባረዋ ቀበሌ ነዋሪ ሲሆን ለባለቤቱ እንደሚገድላት በተደጋጋሚ እየዛተባት ነበር።

በእለተ ሀሙስ በቀን 24/07/2012 በግምት ከንጋቱ 12:00 ሟች አፀደ ዘመድአገኝ በባለቤቷ እንደዛተባትም በአሰቃቂ ሁኔታ በዱላ ጭንቅላቷንና ማጅራቷን ደብድቦ ከገደላት በኋላ ወንዝ ላይ ጥሏት መሄዱ ተገልጿል።

ይህንን አሰቃቂ ድርጊት የሚገልፅ የምርመራ መዝገብ የደረሰው የጉራጌ ዞን ዐቃቤ ህግ መምሪያ የልዩ ልዩ የወንጀል ጉዳዮች ዐቃቤ ህግ የምርመራ መዝገቡ በአግባቡ በመመርመር በተከሳሹ ግለሰብ ላይ የኢ ፌ ዲ ሪ የወንጀል ህግ አንቀጽ 539 (1)(ሀ )ላይ የከባድ የሰው ግድያ ወንጀል ክስ መስርቶበታል።

ክሱ የደረሰው የወልቂጤ አካባቢ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ግራ ቀኙን ሲያከራክር ቆይቶ በቀን 02/13/2012 ዓም በዋለው ችሎት የተከሳሹ ድርጊት እጅግ አደገኛና ነውረኛ መሆኑን ከግምት ውስጥ አስገብቷል።

በተጨማሪም ፍርድ ቤቱ ተከሳሹ ከዚህ ቀደም በ1999 ዓም በሀዋሳ ከተማ የቀድሞ ባለቤቱ በተመሳሳይ ሁኔታ ገድሎ በሀዋሳ ከተማ ከፍተኛ ፍርድ ቤት የእድሜ ልክ እስራት ተፈርዶበት ከሁለት አመት በፊት በይቅርታ ተለቆ መውጣቱን በቅጣት ማክበጃነት ይዟል።

በመሆኑም ሰው መግደል ልማድ አድርጎ የያዘ በመሆኑ: ከዚህ በኋላ እስራት ያስተምረዋል ተብሎ ስለማይታሰብና የኢ ፌ ዲ ሪ የወንጀል ህግ አንቀጽ 117 መስፈርቶች ሙሉ በሙሉ የሚያሟላ በመሆኑ በአጠቃላይ ሌላው የህብረተሰብ ክፍል ሊያስተምር ይችላል ያለውን የሞት ቅጣት ውሳኔ ወስኖበታል ተብሏል።

ውድ አድማጮቻችን እና ተከታዮቻችን የኢትዮ ኤፍ ኤም ስርጭቶችን፣ዜናዎችን እና ሌሎች ዝግጅቶችን ለመከታተል የቴሌግራም ቻናላችንን ይቀላቀሉ። https://t.me/ethiofm107dot8

ኢትዮ ኤፍ ኤም የኢትዮጵያዊያን
ጷግሜ 3 ቀን 2012 ዓ.ም

FacebooktwitterredditpinterestlinkedinmailFacebooktwitterredditpinterestlinkedinmail

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *