ተገቢው ምርመራ ተደርጎ ለተጎጅዎች መፍትሔ ይሰጥ ኢሰመኮ

በሶማሊ እና ኦሮሚያ ክልል አዋሳኝ አካባቢ ላይ በክልሎቹ የጸጥታ ኃይሎች መካከል በተፈጠረ የተኩስ ልውውጥ፣ በሲቪል ሰዎች ላይ የደረሰውን ጉዳት ተገቢ የሆነ ምርመራ በማድረግ ለተጎጂዎች ዘላቂ መፍትሔ መስጠት ያስፈልጋል ሲል ኢሰመኮ አሳቧል፡፡

በካምፓላ ስምምነት መሠረት የመንግሥት የጸጥታ አካላት የሀገር ውስጥ ተፈናቃዮች የሚገኙባቸውን የመጠለያ ጣቢያዎች ደኅንነት አደጋ ላይ ሊጥሉ ከሚችሉ ተግባራት ሊቆጠቡ እንደሚገባም ኮሚሽኑ ገልጧል፡፡

የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) በሶማሊ እና በኦሮሚያ ክልል አዋሳኝ አካባቢ፣ በሁለቱ ክልሎች የጸጥታ ኃይሎች መካከል በተፈጠረ የተኩስ ልውውጥ ምክንያት በአካባቢው የተጠለሉ የሀገር ውስጥ ተፈናቃዮች እና የአካባቢው
ነዋሪዎች መጎዳታቸው አሳሳቢ መሆኑን ገልጧል፡፡

ኢሰመኮ መስከረም 7 ቀን 2016 ዓ.ም. በባቢሌ አቅራቢያ በኦሮሚያ እና በሶማሊ ክልል የጸጥታ ኃይሎች መካከል የተፈጠረውን የተኩስ ልውውጥ በተመለከተ ተጎጂዎችን፣ የኦሮሚያ እና የሶማሊ ክልል የጸጥታ አካላትን፣ የቆሎጂ መጠለያ ሠራተኞችን እና የሆስፒታል ባለሞያዎችን ማነጋገሩን ለኢትዮ ኤፍ ኤም በላከው መግለጫ አሳውቋል።

በአሁኑ ወቅት ግጭቱ የቆመ ቢሆንም፤ በተኩስ ልውውጡ ወቅት ቆሎጂ የሀገር ውስጥ ተፈናቃዮች መጠለያ ጣቢያ የሚኖሩ ቢያንስ ስድስት ተፈናቃዮች ተገድለዋል፣ በርካታ ሰዎች ቆስለዋል እንዲሁም በሌሎች የአካባቢው ሲቪል ሰዎች ላይ የሞት እና የአካል ጉዳት ደርሷል ብሏል፡፡

ስለዚህም ሁለቱ ክልሎች በቅንጅት በመሥራት በአካባቢው ለተከሰተው ግጭት ምክንያት ለሆኑ ጉዳዮች ሰላማዊ መፍትሔ በመስጠት የነዋሪዎችን እና የተፈናቃዮችን ደኅንነት በዘላቂነት የማረጋገጥ ሥራ እንዲሠሩ፣ ለደረሰው ጉዳት ተጎጂዎች እንዲካሱ እና ተገቢ የሆነ ጥንቃቄ ባለማድረግ በሲቪል ሰዎች ላይ ጉዳት እንዲደርስ ባደረጉ የጸጥታ ኃይሎች አባላት ላይ አስፈላጊው ምርመራ ተደርጎ ተጠያቂነት እንዲረጋገጥ ጠይቋል፡፡

የኢሰመኮ ምክትል ዋና ኮሚሽነር ራኬብ መሰለ፣ የመንግሥት የጸጥታ ኃይሎች በተፈጠረው ግጭት ወቅት በሲቪል ሰዎች ላይ ጉዳት እንዳይደርስ ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ የነበረባቸው መሆኑን ጠቅሰው፣ “በተለይም ቀድሞውኑ ከቤት ንብረታቸው ተፈናቅለው ለዓመታት በመጠለያ ጣቢያ ውስጥ አስቸጋሪ ሕይወት ይመሩ የነበሩ የሀገር ውስጥ ተፈናቃዮች ለሞት እና ለአካል ጉዳት መዳረጋቸው አሳሳቢ ነው” በማለት ገልጸዋል።

ምክትል ዋና ኮሚሽነሯ “በአፍሪካ የሀገር ውስጥ ተፈናቃዮች ጥበቃ እና እገዛን አስመልክቶ የተደረገው የአፍሪካ ሕብረት ስምምነት (ካምፓላ ስምምነት) መሠረት የመንግሥት የጸጥታ አካላት የሀገር ውስጥ ተፈናቃዮች የሚገኙባቸውን የመጠለያ ጣቢያዎች ደኅንነት አደጋ ላይ ሊጥሉ ከሚችሉ ተግባራት ሊቆጠቡ ይገባል” ብለዋል፡፡

ኢትዮ ኤፍ ኤም 107.8 የኢትዮጵያዊያን

መስከረም 21 ቀን 2016 ዓ.ም

FacebooktwitterredditpinterestlinkedinmailFacebooktwitterredditpinterestlinkedinmail

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *