የሕዝብ ተወካዮች ውክልና የሚሻርበት መመርያ ገዥው ፓርቲ ተቀናቃኞቹን የሚበድልበት እንዳይሆን ፓርቲዎቹ ስጋታቸውን ገለጹ፡፡

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ፣ የፌዴራልና የክልል ሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት የመረጣቸው ሕዝቦች አመኔታ በሚያጡበት ጊዜ፣ ውክልናቸው የሚሻርበትን ረቂቅ መመርያ፣ ገዥው ፓርቲ ተቀናቃኞቹን ከአባልነት ለማስወገድ የሚጠቀምበት እንዳይሆን ሥጋት እንዳላቸው የፖለቲካ ፓርቲዎች ገልጸዋል፡፡

የወላይታ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ግንባር አባል አቶ ጎበዜ ጎአን፣ በሕዝብ የተመረጡ የፓርላማና የክልል ምክር ቤት አባላትን ለማስወገድ መጠቀሚያ እንዳይሆን የተለየ ጠንካራ አሠራር ያስፈልጋል ብለዋል፡፡

ገዥው ፓርቲ የማይፈልገውን አካል ከምክር ቤት ለማስወጣት መመርያውን ተጠቅሞ ሕግ እንዳይጥስ ምርጫ ቦርድ የተለየ ጥንቃቄ ማድረግ ያስፈልገዋል ነው ያሉት፡፡

የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) ተወካዩ አቶ ማሙሸት አማረ በበኩላቸው፣ በዚህ ሕግ አማካይነት ሐሳባቸውን በምክር ቤቶች ጎላ ብለው የሚናገሩ ተመራጮችን ገዥው ፓርቲ ‹‹አላሠራ ብሎኛል›› በሚል ሴራ እነዚህን ተወካዮች ከአባልነታቸው እንዲሰናበቱ የሚያደርግ ነው ብለዋል፡፡

የኢትዮጵያ ሶሻሊስት ዴሞክራሲ ፓርቲ አባሏ ዶ/ር ራሔል ባፌ በበኩላቸው፣ የሚነሳው የይነሳልኝ ጥያቄ በትክክል የመራጩ ሕዝብ ጥያቄ መሆኑን በምን ማረጋገጥ ይቻላል? የፖለቲካ ግፊት እንዳይሆን በምን ይረጋገጣል ሲሉ ቦርዱን መጠየቃቸውን የሪፖርተር ዘገባ ያሳያል፡፡

የኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ ተጠባባቂ ሰብሳቢ አቶ ውብሸት አየለ፣ በአንድ ተወካይ ላይ የሚመጣ ተፅዕኖ ከገዥውም ይሁን ከተፎካካሪ ፓርቲ የሚመለከቱ ጉዳዮች ቦርዱ በጥብቅ የሚከታተለው ይሆናል ብለዋል፡፡

ኢትዮ ኤፍ ኤም 107.8 የኢትዮጵያዊያን

ጥቅምት 05 ቀን 2016 ዓ.ም

FacebooktwitterredditpinterestlinkedinmailFacebooktwitterredditpinterestlinkedinmail

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *