33ኛዉ የገና ንግድ ትርዒት ባዛርና ፌስቲቫል በየቀኑ ለ13 ሰዓታት ክፍት ሆኖ እንደሚቆይ ተነገረ፡፡

በአዲስ አበባ ኤግዚቢሸን ማዕከል ከታህሳስ 6-27/2016 ዓ.ም ድረስ ሊካሄድ ዝግጅት የተጀመረዉ 33ኛዉ የገና በዓል ባዛርና ፌስቲቫል በየቀኑ ለ13 ሰዓታት ክፍት ሆኖ ይቆያል ተብሏል፡፡

ባዛሩ በሚካሄድባቸዉ 22 ቀናትም በአማካይ 15 ሺህ ሰዎች ይጎበኛሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ የሴንቸሪ ፕሮሞሽንና ኤቨንትስ ባለቤት እና ስራ አስኪያጅ አቶ ዘዉገ ጀማነህ ተናግረዋል፡፡

የጎብኚዎች ቁጥር እንደመጡት እቃዎች እና እንደ ህዝቡ ፍላጎት ከፍ ዝቅ ሊል ስለሚችል፣ የተጋነነ አድርገን ማስቀመጥ አልፈለግንም ያሉት ስራ አስኪያጁ ፤በዚህም በአማካይ 15 ሺህ ጎብኚዎች ይገኛሉ ብለን እንጠብቃለን ብለዋል፡፡

እስካሁን ድረስ ምርቶቻቸዉን ለመሸጥ የተመዘገቡ ሰዎች ቁጥር ከ3መቶ በላይ ደርሷል ያሉም ሲሆን ፤ቁጥሩ ከ5 እስከ 6መቶ ሊደርስ እንደሚችልም ተናግረዋል፡፡

የቦታ ክፍያዉን ብዙ ጥናት አድርገንበት ከ45ሺህ ብር ጀምሮ እንዲሆን አድርገናል፣ ነገር ግን እንደ ቦታዉ ስፋት የገንዘብ መጠኑ ከ50-55ሺህ ይሆናል ነዉ ያሉት፡፡

ባዛሩ የሚካሄድበት የአዲስ አበባ ኤግዚቢሸን ማዕከል እና የገበያ ልማት ድርጅት ግቢ፤ ቦታዉን የማስዋብ ስራ መስራቱን የገለጸም ሲሆን በ3መቶ ሺህ ብር ወጪ 10ሺህ ሄክታር የመስፋፊያ ስራ እየተሰራ መሆኑም ተገልጿል፡፡

ሴንቸሪ ፕሮሞሽን እና ኤቨንትስ 25ኛ ዓመት የምስረታ በዓሉንም የሚያከብር መሆኑን ባለቤቱ አቶ ዘዉገ ጀማነህ የተናገሩ ሲሆን፤ የፋሲካን ኤክስፖ ለማዘጋጀት ጨረታዉን ማሸነፉንም ጨምረው ገልጸዋል፡፡

በእስከዳር ግርማ

ህዳር 19 ቀን 2016 ዓ.ም

FacebooktwitterredditpinterestlinkedinmailFacebooktwitterredditpinterestlinkedinmail

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *